Friday, January 13, 2017

አማራጭ የሌለው ምርጫ

አማራጭ 
አማራጭ
አማራጭ...
በል እንጂ አማራጭ የማይፈልግማ ማን አለ? የምን አማራጭ ነው?
አማራጩማ ከጫጫታ ርቀህ፣ ከወከባና ከጥድፊያ ኑሮ ወጥተህ፤ በመኪናና ከሞተሮች ጩኸ ት ወዲያ ሆነህ፤ በከብቶች ድምጽ በለመለመው መስክ ላይ እየተዝናናህ፤ ከጓሮህ እያረስክ ከኬሚካል ነፃ በሆነ ፍራፍሬና ምግብ እየተመገብክ፣ ማራኪ መልካምድራዊ አቀማመጥ እና ተፈጥሮአዊ ውበቶችን እያደነቅህ ትኖራለህ ወይስ
በመኪና ጢስ፣ በሰዎች ሁካታና ግርግር በተሞላ መንገድ ላይ እየተጓዝክ፣ ከእንቅልፍህ ስትነሳ የመኪናው ጩኸት፤ ስትተኛ የሰካራሙን እብደት፣ ስትመገብ የታሸገ የፋብሪካና የኬሚካል ውሁድ ያለበት፤ ስትጠጣ ከፊት ለፊትህ ለካንሰር ያጋልጣል የሚል ማስታወቂያ በቴሌቪዥንህ ወይም በራዲዮና እየሰማህ መኖር ይሻልሃል?
ምን ያለው ቀልደኛ ነህ እባክህ? መች ጠላሁትና አንተ ምትለኝን የገጠሩን ኑሮ አይደለም? ከተማው ስቦኝ ነው ከትሜ የቀረሁት። ብፈልግስ እንኳ ስራዬን ጥዬ አልሄድ ወደ ገጠር። ልጆቼም ለምደዋል ከቴክኖሎጂው ጋር ውለው ማደሩን፤ ለእነሱ ገጠር ማለት እስር ቤት ሆኗል ዘመዴ። እስቲ ማን ይሙት የትኛዋ ልጄ ነች በየቀኑ ከብቶችን ተንከባክበሽ፤ ወተት እያለብሽ፤ በገጠር እየሰራን እንደግ ብትባል የምትሰማ ትልቋናት? ወይስ ትንሿ? አዬ! እማይሆነውን? ይልቁንስ ባለፈው... ገጠር ዘመዶቼን ልጠይቅ ወደ ይርጋአለም ሄጄ ነበር። እናልህ ቆይታዬ ጥቂት ቀንም ብትሆን አየሩን መለካምድሩን ተፈጥሮውን ባጠቃላይ አድንቄ ነው የመጣሁት። ሁሌም አዲስ ነው የሚሆንብኝ። እነርሱጋ የ50 ዓመቱ የእድሜ ባለጸጋ ውሎው በነፋሻማው መስክ በመሆኑ የ30 ዓመት ወጣት መስሎ ታየዋለህ። ድሮ ድሮ እኮ ስለገጠሩ አየሩ፤ መለካምድሩ ነበረ ጨዋታው፤ አሁን አሁን ደግሞ በገጠሩ ሁሉ ሞልቶ እየተባለም አይደል። በገጠር ሀብት እያፈራ ልጁን ዩኒቨርሲቲ ልኮ የሚያስተምረው፤ ትራክተሩን ገዝቶ የሚያርሰው አርሶ አደር ቤት ይቁጠረው። የተጎዳንማ እኛ ነን እንጂ ከተሜዎች ወይ ከገነዘብ ወይ ከጤናም አልሆንን።
እናስ ምን ሆነህ ነው አንተ ከተማ ለከተማ የምትሯሯጠው? በል ጃል አማራጭህን አይተህ መሄድ ነው እንጂ። አዬ! የኛ ነገር «ከሞኝ ደጅ ሞፈር ይቆረጣል ነው ነገሩ»። የገጠሩ ወጣት ያን የመሰለ እንቁ መሬት ትቶ በስደት በአረብ አገሮች ህይወቱን ያጣል። ነገር ግን የገጠሩ ወጣት ትቶት ሄደውን መሬት አጅሬ ፈረንጅ፤ ኢንቨስተር ሆኖ ሰርቶ ያሰራበታል። እናስ ገጠሩስ ያንተው አይደል? ሄደህ ለነፍስም ለስጋም የሚሆን ነገር እማታገኝበት ምነው!?
እንግዲህ ገጠር መሄዱን ብፈልግም አልችልም፤ የሚይዙኝ ብዙ ነገሮች አሉ እያልከኝ አይደል። ታዲታ አማራጭ የሌለው ምርጫ ከተማውን ገጠር ቀመስ ማድረግ ነው። እንዴት ሳትለኝ እኔው ልንገርህ። ምን ይባላል መሰለህ «አንድ የምትፈልገው ነገር ወደ አንተ የማይመጣ ከሆነ አንተ ራስህ ወደ እርሱ ሂድ» ይባላል። የወደድከውን ከተማ የምትኖርበትን ቀዬ በአትክልቶችና የልምላሜ ምልክት በሆኑ ተከሎች በማስዋብ ንጹህ አየር መማግ አንደኛው የመልካም ገጠራማ አካባቢ ንጹህ አየርን ለመሳብ የሚያስችል አይነተኛ ዘዴ«ሞደ ፌክ» ነው። ስለዚህ ከኬሚካልና ከአላስፈላጊ ንጥረ ነገሮች የጸዱ የጓሮ አትክልቶችን በቤትም ሆነ በጓሮ አካባቢ መትከልና መጠቀም ያስፈልጋል። ይህ ጤንነትን ብቻ ሳይሆን መንፈስንም የሚያድስ ስራ ይሆናል።
እንኳን ለአትክልትና ቆሞ ለመቆዘሚያም የሚሆን ጓሮም የለኝ፤ እንዲያው የጋራ መኖሪያ ቤት ላይ ነዋሪ ነኝ የምትል ከሆነ ደግሞ። ጓሮም የጋራ አለው እልሃለው። ብትችል ብትችል በረንዳህ ላይ በጥሩ ሁኔታ በተዘጋጁ እቃዎች አትክልቶችን መትከል ከዚያም ውጤቱን በትንሹም ቢሆን ማየት ትችል የለ።
በሁለተኛ ደረጃ ላይ እንደ ስሙ ቆሻሻ የሆነውን የቆሻሻ አወጋገድ ሥርዓት ፈር ማስያዝ ነው። በየአካባቢው ያለው አፍንጫ የሚሰነፍጥ መጥፎ ጠረን በአብዛኛው ከየቤቱ በሚወጣ ተረፈ ምግብም በለው ሌላ በየቦታው ይዝረከረክና ለሳይነስ ብሎም ለጉንፋን በሽታ የሚያጋልጠው እሱ ነው። በተለይ ከበዓል ሰሞን በኋላ በኛ ከተሜዎች መንደር አለማለፍ ነው የሚሻለው። እኔማ በሰማይ በርሬ ቤቴ ብገባ እመርጥ ነበር? ዳሩ «አልበር እንዳሞራ» ሆነብኝ እንጂ። ታዲታ ልክ እንደ ቀን ተቀን የምግብ አወሳሰዳችን ጥንቃቄ ያለው የቆሻሻ አወጋገድ ሥርዓት በየሰፈሩ ማስፈን ሳያስፈልግ አይቀርም።
ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ቆሻሻ የሚያነሱ ወጣቶች ስራ ፈጣሪ ሆነው ቢንቀሳቀሱም መቼም የውሃ መውረጃ ትቦውን ነገር አንተም ታውቀዋለህ ውስጡን ለቄስ ነው። መቼም እነዛ የረጋ ቆሻሻ ውሃ የያዙ የመንደር ውሃ መፍሰሻ ቦዮች ላይ አዳልጦት የገባ ሰው «ተንቀሳቃሽ ከሰል» መሰሎ መውጣቱ አይቀሬ ነው። ምክንያቱም ውሃው ወደ ጥቁርነት ተቀይሮ የለ!? እፍ... ያንገሸግሻል ሽታውማ። እንዲያ ነው ነገሩ፤ ገጠር ዝም ብሎም አይገኝም። እንደገጠሩ ከተማውም መስተካከል አለበት ተፈጥሮን በልኳ ለማግኘት።
ሌላው እንግዲህ የገጠሩን ሰላማዊ መንደር በእውንህ ለማግኘት ብሎም በአካባቢ ያሉ ጫጫታዎችንና ሁካታዎችን ላለመስማትና ከእነርሱም ለመራቅ የግድ ጥብቅ ደን ውስጥ መግባት አይጠበቅብህም እንዲያው ህጉን ጠበቅ ስርአቱን ጠንከር እንዲል በማድረግ በየመንገዱ ይሄ ካሴት ወጥቷል እያሉ ከሚለፍፉት ባለመኪኖች ጭምር አደብ እንዲይዙ መጣር ነው። እናም ነገሩ እስከ ቤት ድረስ ይዘልቃል ። ታዲያ በውጭ የሚያልፍ ብቻም አይደል ጸጥታ ማስከበሩ። እናስ ከዚያ በኋላ ከስራ ሲመለሱም ሆነ ወደ ሥራ ሲሄዱ ለአይን ማራኪ አካባቢ ማየት መቻል ከተሜን ከነ ሙሉ ትጥቁ ገጠር ቀመስ አደረገው ማለት አይደል። ይሄ ነው እንግዲህ አማራጭ የሌለው ምርጫ ከተሜ።

ጉርሻ ሞልቷል ባገሩ


በሬ ካላረሰ ባል ካላጎረሰ ወዲያ ፈቶ መልቀቅ ነው እንዲሁም ፍቅርና ጉርሻ ሲያስጨንቅ የተሰኙ አባባሎች በኢትዮጵያ የተለመዱ ናቸው። በርግጥ ከአባባሎቹ በተጨማሪ የቤተሰብ ጉርሻ እበላ ያደገውን የትየለሌ በመሆኑ ቤት ይቁጠረው። የጉርሻ ነገር ሲነሳ ግን ትዝ የሚለኝ ልጅ እያለሁ የማልወደው የምግብ አይነት እንኳን ቢሆን አባቴ ካጎረሰኝ እንደሚጣፍጠኝ ነው።
ታዲታ እንደ ወላጅ እና ዘመድ አዝማድ ሳይሆን ልክ ምግብ ቤት እንደሚባሉት ጉርሻ ቤቶች ተፍተው በአዲስ አበባ ውስጥ ስራ ከጀመሩ ሰነባብተዋል። የዛሬ አራት እና አምስት አመታት ወሬው ሲሰማ ጉድ ሳይሰማ መስከረም አይጠባም ተብሎም ነበው። አንደኛው ጉርሻ ቤት በተዘጋጀለት ጠባብ መስኮት አማካኝነት የእማማን በጉርሻ ሁለት ብርዎች ከፍለው ያገኙታል።
በርካታ ደንበኞች ያሉት ይህ የጉርሻ ምግብ ቤት ሰባተኛ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ የሚገኝ ሲሆን «ወረፋ ደርሶን ካገኘነው የምግብ አምሮታችንን ጋብ ያደርግልናይ» ይሉታል የቀመሱት ሰዎች።
ከምግብ ቤቷ አጠገብ ቁጭ በሰሃን የተቀበለውን አንድ ጉርሻ ሲያጣጥም ያገኘሁት ወጣት «አቡሌ እባላለሁ» አለኝ
እኔም ለማወቅ እንደጓጓ ሰው ጠጋ ብዬ እንዴት ነው የጉርሻው ነገረ አልኩት።
በየቀኑ የእማማን አንድ ጉርሻ በሁለት ብር ገዝቼ መክሰስም በለው ቁርስ ብቻ ተመችቶኛል እያለ በደስታ አወጋኝ። ሁል ጊዜ እዚህ አካባቢ ብትመጣ ጉርሻ ባለበት ሰዓት አካባቢው በወጣት አንዳንዴም በአዛውንቶች ሰልፍ ተሞልቶ ታገኘዋለኝ አለ። ከዚህ ቀደም ከአምስትና ስድስት አመታት በፊት አንድ ጉርሻ በ25 ሳንቲም እንበላ ነበረ አሁን ተወደደ ተብሎ ሁለት ብር ገብቷል ብሎ አከለበት። እናም ሆድን አስጨንቆ ከመብላት እንዲህ ጎረስ እያደረጉ መሄድ መልካም ነው የሚል ቀልድ አዘል ሃሳቡን ጣል አድርጎ ወደ ስራ መግባቴ በቃ ቻው ብሎኝ እብስ አለ።
አንዱ ወዳጄ ደግሞ እዛው አካባቢ ዞር ዞር ብትል ሌላም የጉርሻ አይነት ታገኛለህ አለኝ። ምን አይነት ደግሞ ከዚህ ሌላ የሚል ጥያቄዬን ያነሳሁበት ወዳጄ ሲመልስልኝ በመስኮቷ የሚሸጠውን ጉርሻ ምግቡን የሚሰሩት እዚያው ምግብ ቤቱ ውስጥ ነው። ሌላኛውን የጉርሻ አይነት ግን ከሆቴሎችና ከዩኒቨርሲቲዎቸ ተርፎ ከሚመጣ ምግብ ላይ የሚሸጥ ነው አለኝ። እናም በፌስታል በፌስታል ምግቡ ይቀመጣል አንድ አንድ ጊዜ መጉረስ ነው ቀጣዩ ተግባር እያለ አስረዳኝ። የተረፈው ምግብ ከተለያዩ አይነቶች ተቀላቅሎ የሚመጣ በመሆኑ ከየትኛው የምግብ አይነት እንደሆነ የተሰራው እርግጠኛ መሆን ባይቻልም እድል ካለ ግን ስጋ ሊገኝበት ይችላል ብሎኛል ወዳጄ።
ነገር በአይን ይገባል ነውና ጉዳዩን ለመመለከት ወደስድስት ኪሎ ዩኒቨርሲቲ አካባቢ ጎራ ብዬ ነበር። «በተለምዶ 'ቡሌ' ይሉታል ወጣቶቹ ይህ ምግብ እኛ ደግሞ በመሸጥ መተዳደሪያችን አድርገነዋል» አሉኝ ከትልቅ ፌስታል ለተመጋቢው በጭልፋ እያወጡ ምግቡን የሚሸጡት አንድ ባልቴት። እናም «ጎራሽ ሞልቷል ግን ደህኗ ጎራሽ የተባሉ ወጣቶች በመምጣታቸው አሰራሩ እንዲቀየር ምክንያት ሆኗል» ሲሉ ገለጹልኝ።
እንዴት? አልኳቸው አሰራሩ መቀየሩን እንዲያብራሩልኝ
በፊት በፊት ጉራሹ በሙላ ገንዘቡን ይከፍልና እራሱ ነበር ከፌስታሉ ውስጥ የሚያነሳው። አንዳንድ ወጠምሻ ጎራሾች ግን በአንዴ የሚያነሱት ከፍተኛ መጠን ያለው ምግብ በመሆኑ ለኪሳራ እየተዳረግን ተቸግረን ነበር። በመሆኑም አንድ መላ ተዘይዶ እየተሰራነት ይገኛል። ይኀውም እኛ እራሳችን ማለትም ሻጮች በእጃችን ልክ ለተመጋቢው አንድ አንድ ጉርሻ እያነሳን እንሰጣቸዋለን። ከፈለጉ በሰሃን ይወስዳሉ ከፈለጉ በእጃቸው ተቀብለው ይጎርሳሉ። ይህ ታዲያ እኛንም ከኪሳራ ተመጋቢውንም ከአድልኦ አሰራር አርቆናል ማለት ነው።
ቆይ ምግቡን ገዝታችሁት ነው የምታመጡት? ማለቴ ለኪሳራ ተዳረግን ስላሉኝ ነው።
ከየሆቴል ቤቱ የተረፈውን ምግብ እየገዛሁ ነው በተጨማሪ ሌሎች ዩኒቨርሲቲ ውስጥ የሚሰሩ ምግቡን ስለሚያወጡት እነሱ እንኳን በነጻ ነው። ብቻ አስራ ሁለት ሰዓት ላይ ስድስት ኪሎ ዩኒቨርሲቲ አካባቢ ብትመጣ ምድሩን ሁሉ ጉርሻ ተመጋቢ ሞልቶት ታገኘዋለህ።
«የምግቡ ጣዕም ሽታው እርጉዞች ሳይቀር የሚያሰኛቸው እና የሚያምራቸው ነው አንዳንዴ እኛ ብቻ ሳንሆን ነፍሰ ጡሮችም መጥተው ይጎርሳሉ» ሲል የነገረኝ ደግሞ በዩኒቨርሲቲው አካባቢ ለጉርሻ ተሰልፎ ያገኘሁት ወጣት ነው። «እኔ እንኳን እራቴን እዚሁ ሁለት ጉርሻ በልቼ ነው ወደ ማደሪያዬ የምሄደው በየቀኑ ይህን ስለማደርግ ደንበኛ አሉኝ። አንዳንድ ጊዜ ከጉርሻው ካልተመቸን ሰብሰብ ብለን ከጓደኞቼ ጋር አዋጥተን ምግቡን እንገዛና በህብረት እንመገባለን። ይህም በሽሚያ እና በጥድፊያ የሚከናወነ በመሆኑ በርታ ብሎ እጁን ያልሰደደ ከአንድ ጉርሻ በላይ የማያነሳበት አጋጣሚ ይፈጠራል። ስለዚህ በህብረት በምንመገብበት ጊዜ በደንብ አድርጌ ነው ጉርሻዬን የማነሳው» ሲል የአመጋገቡን ልምድ ገልጾልኛል።
ህጻን ልጇን ይዛ ምግቡን ስትገዛ የነበረች እናት ደግሞ «እኔ ከልጄ ጋር አረፍ ብዬ መብላት ስለምፈልግ ለሁለታችንም የሚሆነውን በአምስት ብር እገዛና መንገድ ዳር ሆኜ እመገበዋለሁ። ጎዳና ላይ የማድር በመሆኑ ለእኔም ለልጄም የሚቀርብልን ርካሹን ምግብ ገዝተን እየተመገብን እንኖራለን ትላለች። ጉርሻ ስፈልግም እዛው በልቼ እሄዳለሁ። አሁን ምግብ ሻጮቹ እራሳቸው የሰፈሩትን ስልሚሰጡት እኩል እኩል ይደርሰዋል ሁሉም። ብላለች። የወጣት ወንዶች የሰልፍ ላይ ግፊያና ጩኀት ስለሚያስቸግራትም በጊዜ መጥታ ተራ እንደምትይዝ ነው የነገረችኝ።
ምግቡን በመሸኝ የምትተዳደረውን ወጣት እዚ አካባቢ በጣም ፍቅር አለ አንዱ በርከተ አድርጎ የገዛውን ለሶስት ለአራት ይበላል። በሌላ በኩል እኛም ለቸገረው አንሰስትም መርቀን ነው የምንሰጠው ብላኛለች። አንድ ጉርሻ በእኔ ወጪ ተመገብ ብላ የጋበዘችኝን ወጣት እኔም ላመስግናት ካላት ላይ ቀንሳ ለሌላው መስጠቱን በተግባር ላሳየች። መልካም ጊዜ

ከባለጌ ፍቅር የንጉስ ቁጣ ይሻላል

ድሮ ድሮ ያኔ መጽሃፍ በጥራዝ መታተም በጀመረበት አፍላ የዘመናዊነት ጊዜ ነው አሉ። ልጆች ከዘመናዊ ትምህርት ቤት ይልቅ ከብት ማገድ እና ወላጅ ማገዝን ብቻ ስራዬ ባደረጉበት ጊዜ። አንድ ጊዜውን በእርሻ ስራ እና በማህበራዊ ኑሮ እያሳለፈ ከሰኔ እስተ ሰኔ የቤተሰቡበ ቀለብ ለመሸፈን ውሎው ከማሳው ላይ ያደረገ አርሶ አደር ነበር። ቀን ከእርሻው መልስ ሲያሻው ጫካ ለአደን ሲያሻው ደግሞ የግቢው እጥር በማጠባበቅ ሲታትር የሚውለው ይህ በስራ የተወጠረ ሰው ማታም ቤቱ ሲገባ አባወራነቱ ይመጣል መሰል ሁሌም ኮስታራ ፊቱን ለልጆቹ እንዳሳየ ነው።
እንዳሁኑ ቴሌቪዥን ወይም ራዲዮን ያለ የሚዝናናበት አማራጭ ባለመኖሩ ነው መሰል አብዛኛውን ጊዜ እስኪተኛ ድረስ ቤቱን በብርሃን በምትሞላው ኩራዝ ላይ ያፈጣል። አሊያም እርስ በርስ የሚጨቃጨቁ ሶስት ልጆቹን በቁጣ አደብ እንዲገዙ ሲነታረክ ወይም ቀን ምን ምን ስራ እንዳከናወኑ ሲጠይቅ መተኛ ሰዓቱ ይደርስለታል። ነገም እንደዛው ከነገወዲያም ብቻ ምን አለፋችሁ የዘመድ ወይም የጎረቤት ሰርግ ከሌለ በስተቀር ጨዋታ እና ቀልድ ባለፉበት የማለፍ እድል የለውም።
ሚስቱም ብትሆን ኮስታራ ፊቱን በመፍራት ይሁን ከአክብሮት ብቻ ሰው ፊት አብራው ስትጫወት እና ስትስቅ አትታይም። እንደውም አስፈላጊውን ነገር ማለትም እጅ ማስታጠቡን፣ ምግብ ማቅረቡን፣ አንዳንድ ለቤቱ አስፈላጊ የሆኑ ጉዳዮችን ከማማከር ውጪ አደግድጋ ነው በአንቱታ ጥሪ ታጅባ ነው የምትቀበለው። እናም ከዕለታት በአንደኛው ቀን ለአገሩ እንግዳ የሆነ ከተሜ ኑሮውን ሳይታሰብ በድንገት አኮፋዳውን ብቻ ይዞ ከተፍ ይላል። አጅሬ ምስኪን አርሶ አደር ቀን ለስራ የተጠቀመበትን ሞፈር እና ቀምበር ከነበሬዎቹ እየነዳ ወደ ገቢው ሊገባ ሲል ፊት ለፊት ይገጣጠማሉ። የአገሩ ደንብ ነው እና እንግዳውን አንዳንድ ጥያቄ ካነሳሳለት በኋላ በቤቱ እንዲያድር ግብዣ አቀረበለት። እንግዳውም በሃሳቡ ተስማምቶ በጎጇቸው ለማደር ተስማማና ወደ ውስጥ ዘለቁ።
እንግዳው ጨዋታ አዋቂ የሚባል ሰው ነበርና እናም ቀስ በቀስ መግባባቱ መላመዱ ሲቀጥል ጨዋታው የጣማቸው መላው የቤተሰቡ አባላት በደስታ ተሞልተው ወጋቸውን ያጣጥሙ ጀመር። አርሶ አደሩም እሰከዛሬ አይቶት የማያውቀውን የልጆቹን ሳቅ ባየ ጊዜ ይበልጥ የልጆቹ ፍቅር ጨመረበት። በዚህም ጊዜ ለእንግዳውም አንድ ወግ ሊያጫውተው ልቡ ሻተና ንግግሩን ቀጠለ።
«ይገርምሃል ንጉሱ ከአመት በፊት ቀዬውን ሊጎበኙ መጥተው ከተዋወቁኝ በኋላ አንድ ጥያቄ በባለሟላቸው አማካኝነት ላኩብኝ። መልዕክቱም 'ከሶስቱ ልጆችህ መካከል አንዱን ላንተ አስቀርና ሁለቱን መሃል አገር ወስጄ ላስተምራቸው በቅርቡ የተከፈተ ጥሩ ትምህርት ቤት አለና እዚያ እውቀት እየገበዩ ቢያድጉ ለአገር መከታ ይሆናሉ። ክረምት ክረምትም እየመጡ እንዲጎበኙህ አደርጋለሁ' የሚል ነበር። ወዲያው እንደሰማሁ ምን ሃብት አለኝና ሃብቴም ልጆቼ ናቸው እንቢኝ አሻፈረኝ በሚል መንፈስ ለባለሟሉ ትንሽ ይደጉ ብዬ ነው እንጂ ልድራቸው አስቤ ነበር የሚል መልዕክት ላኩላቸው። አዬ ንጉስ ታዲታ ጉብኝታቸውን ሲጨርሱ አስጠርተውኝ አሻፈረኝ ማለቴ እርሳቸውን አለማክበር ብቻ ሳይሆን የልጆቹንም እድል ማበላሸት መሆኑን ተናግረው። በሃይለ ቃል 'ያንተን እድል ብታበላሽም የሌሎቹን ልጆች ወስጄ አስተምራለሁ ምን ይጎልብኛል። ሌላ ጊዜ ስመጣ ግን ብትከለክለኝ ውርድ ከራሴ' ብለው ከፊታቸው እንድጠፋ በቁጣ አንባረቁብኝ» ይለዋል
ቀጠል አድርጎም «ስንቱ ልጁን ለከተማ አስኳሏ ሲያስሞሽር እኔ ሚስቴን እና ልጆቼን ባለማማከሬ እድል አበላሸሁ። ይሁንና መች ይመጣሉ እያልኩ በጉጉት ሰጠብቅ የትምህርት እድሜያቸው አልፎ የዋሸሁለት ተዳር እንዳይደርስ ፈራሁ» በማለት ያጫውተዋል።
እንግዳውም ነገሩን ካዳመጠ በኋላ የልጆቹ ከተማ መሄድ እንደሚጠቅመው ያስረዳው ጀመር። ልጆቹን ንጉሱ ለትምህርት መውሰዳቸው ነው እንጂ ከተማ ቢሄዱ ስራ እንደሚያገኙ እና ሃብት በሃብት ሆነው ኑሮውን እንደሚያሻሽሉለትም ይመክረው ጀመር። በተለይም ትንሹ ልጁ ሲያየው ቀልጣፋ እና ንቁ በመሆኑ አይኑን አሳርፎበታል።
«በጣም ስለወደድኩህ እና በመስተንግዶህም ስለተደሰትኩ አንደ ውለታ ልውልልህ እፈልጋለሁ። ይኸውም ትንሹ ልጅህን ለማይረባ ጉዳይ ለትምህርት ሳይሆን ለደህና ቁም ነገር አስቤልሃለሁ። ያንተን ፍቃደኝነት ላጣራ ብዬ ነው እንጂ ከተማ ለሱ የሚሆን ብዙ ስራ አለ። በተለይም ብዙ ገንዘብ የሚያሳፍሱ ቀላል ስራዎች በመኖራቸው ወደፊት በልጅህ አማካኝነት ዲታ የምትሆንበት አጋጣሚ አለ። እናም ትንሹን ልጅ ልውሰድና ሃብታም ላድርገው» ይለዋል።
ነገሩን በጥሞና ሲያዳምጥ የነበረው አርሶ አደር «ድሮም ለልጅ ገንዘብ ሳይሆን እውቀት ነው የሚያስፈልገው በፊት ተሳስቼ ባስቀራቸው አሁን ልሰጥህ አልችልም። ስላሰብክልኝ አመሰግናለሁ ግን ካንተ ሃሳብ ይልቅ የንጉሱ ቁጣ ይሻለኛል» በማለት አሳፍረው መለሱት። አጅሬ እንግዳ ለካ ሲጣራ በየቤቱ እየገባ ህጻናትን ለስራ የሚመለምል ኖሯል። እናም ሰው እንዴት ልጅ ወልዶ ለሰው ልጅ አያዝን በሚል አጀብ ተባለ በአገሩ።

Featured post

ለሰብአዊ መብቶች ጥሰት ተጠያቂነትን በማረጋገጥ፣ የሕግ በላይነትን በማስፈን፣ መንግሥትና የስራ አስፈጻሚ አካላቱ በመሉ ለሰብአዊ መብቶች መከበር፣ መጠበቅና መሟላት ያላቸውን ቁርጠኝነት እንዲያሳዩ ልዩ ትኩረትና ክትትል ይሻል

                    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በየደረጃው ያሉ የመንግስት አስፈጻሚ አካላትና ኃላፊዎች ላይ የቅርብ ክትትል በማድረግ ለሰብዓዊ መብቶች መከበር አስተዋጽኦ ሊያደር...