Tuesday, November 14, 2017

እንቦጭ እና አባይ ሳይገናኙ...

የአባይ ተፋሰስ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ የወንድወሰን መንግስቱ የአንቦጭ አረም የአባይ ግድብ ላይ ከደረሰ አገዳው የከፋ እንደሚሆን ያስጠነቅቃሉ፤ በፍጥነት የመራባት ተፈጥሯዊ ባህሪ ያለው እንቦጭ አረም የህዳሴ ግድብ ላይ ሊራባ የሚችልበት እድል አለ ይላሉ። ጣና ሐይቅ እና አባይ ወንዝ ላይ የሚያደርሰው ጉዳት በተጨማሪ በቀጣይ ምቹ ሁኔታ ከተፈጠረለት ወደ ህዳሴው ግድብ የማይደርስበት ምክንያት አይኖርም። በተለይም የአረሙ በስፋት ግድቡ ላይ ከተራባ ውሃውን ከመሻማት በተጨማሪ ወደ ሃይል ማመንጫ ተርባይኖች በመግባት የኃይል መቆራረጥ እክል የመፍጠር አቅም አለው። በመሆኑም ለመጤ አረም መስፋፋና ለስነምህዳሩ መጎዳት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያላቸው የሚከሰቱ የተከላ መሬቶችን እና ትላልቅ ደለሎችን በአባይ ወንዝ ተፋሰስ ላይ ከወዲሁ እንዲያገግሙ ማድረግ ይገባል።

 

አሁን ላይ ማህበረሰቡን በማሳተፍ በእጅ የሚከናወን እንቦጭ አረም የማጥፋት ተግባር ለአረሙ መራባት እድል እንደሚሰጥ ነው፤ አረም ነቀላው በልማዳዊ መንገድ መከናወኑ ደግሞ ስሮቹና ቅጠሎቹ በቀላሉ በእጅ ተበጥሰው ውሃ ውስጥ እንዲንሳፈፉ ያደርጋል። አረሙ በባህርይው በስሩ፣ በቅጠሉ፣ እና በግንዱ እንዲሁም አበባ ሲያብብ ደግሞ
በፍሬው የሚራባ በመሆኑ በሚነቀልበት ወቅት በቀላሉ ከሐይቁ ወደ ወንዙ ተፋሰስ ክፍል እንዲጓጓዝ እድል ሊፈጠር ይችላል።

በመሆኑም አረሙ ከሐይቁ ግድቡ ለመድረስ ከ800 በላይ ኪሎመትሮች የሚፈጅበት ቢሆንም በውሃ ላይ አካሉ የሚጣል ከሆነ በአጭር ጊዜ ውስጥ ግድቡ ክልል የመድረስ እድል አለው። በኤሌክትሪክ ማመንጫ ግድቡ አካባቢ አነስተኛ ደለል የሚያገኝ ከሆነ በቀላሉ ሊራባ ይችላል። በመሆኑም ቅድመ ጥንቃቄው ስራ በተፋሰሱ አካባቢ እና በግድቡ ላይ ማጠንከር ይገባል። በተለይ በየትኛውም የተፋሰሱ አካባቢ አነስተኛ መጠን ያለው አረም በሚታይበት ወቅት አስፈላጊውን እርምጃ በመውሰድ እግር በእግር እየተከታተሉ ተቀናጅቶ ማጥፋት ተገቢ ነው። ለዚህም በቀጥታ ከሚመለከታቸው አካላት በተጨማሪ ህብረተሰቡ ዋነኛውን ድርሻ ሊይዝ ይገባል።

በቀጣይም እንቦጭን የስርጭት አድማሱን እንዳታስፋፋ የአባይ ወንዝ መፍሰሻ አቅጣጫን ተከትሎ ጥብቅ ፍተሻና ቁጥጥር ማድረግ ያስፈልጋል። ክትትሉን በማጠናከርም የትኛው ቦታ ላይ እየተራባ እንደሚገኝ በመለየት የመራባት ሂደቱን መቀነስ ይቻላል። ስራው በሰዎች እጅ ብቻ መከናወኑም ስርጭቱን ሊያባብሰው ስለሚችል የማጥፋት ስራው በዕውቀትና በቴክኖሎጂ ሊደገፍ ይገባል። በህብረተሰብ ንቅናቄ ብቻ ችግሩን ለመቅረፍ የማይቻል በመሆኑ ስሩ በአግባቡ እንዲነቀልና ከተነቀለም በኋላ አረሙ በአግባቡ የሚወድምበት መንገድ መመቻቸት አለበት። ህብተሰቡ መንግስም ሆነ በውጭ የሚገኙ ሰዎች አረሙን ለማጥፋት እያደረጉት ያለው ጥረት አበረታች ነው። የአማራ ክልል ዘመናዊ ቴክኖሎጂ የሚጠቀም ማሽን መረጣና ግዢ እያከናወነ በመሆኑ ማሽኖቹ ሲገቡ የችግሩ ጉዳት ለመቀነስ እንደሚረዳ ይጠበቃል።

No comments:

Post a Comment

Featured post

ለሰብአዊ መብቶች ጥሰት ተጠያቂነትን በማረጋገጥ፣ የሕግ በላይነትን በማስፈን፣ መንግሥትና የስራ አስፈጻሚ አካላቱ በመሉ ለሰብአዊ መብቶች መከበር፣ መጠበቅና መሟላት ያላቸውን ቁርጠኝነት እንዲያሳዩ ልዩ ትኩረትና ክትትል ይሻል

                    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በየደረጃው ያሉ የመንግስት አስፈጻሚ አካላትና ኃላፊዎች ላይ የቅርብ ክትትል በማድረግ ለሰብዓዊ መብቶች መከበር አስተዋጽኦ ሊያደር...