ያገለገሉ የህክምና ቁሶች መልሰው ጥቅም ላይ እንዳይውሉ ምን ይደረግ?
የከተማ ልማትና ቤቶች ሚኒስቴር የደረቅ ቆሻሻ አያያዝ፣ አሰባሰብና አወጋገድ ስታንዳርድ (ደረጃ) አውጥቷል። በስታንዳርዱ የትግበራ ማንዋል ቁጥር 06/2007እንደተገለጸው
ደግሞ ከህክምና ተቋማት የሚመነጩ አደገኛ ቆሻሻዎችን ለማከም ወይም ለማስወገድ አነስተኛ መጠን ያለው የቆሻሻ
ማቃጠያ ፋሲሊቲ በየተቋማቱ መገንባት ታሳቢ መሆን አለበት። ይህም መልሰው ጥቅም ላይ ቢውሉ ችግር ሊያመጡ የሚችሉ
የህክምና መገልገያዎች ዳግም ጥቅም ላይ እንዳይውሉ ይረዳል።
በትግበራ ማንዋሉ ላይ በጀርመን ዓለም አቀፍ ትብብር ድርጅት(ጂአይዜድ) በሚደገፍ
ፕሮጀክት አማካኝነት በተመረጡ ሆስፒታሎች በተደረገ ፍተሻ ከጤና ተቋማት የሚመነጭ አደገኛ ቆሻሻ አያያዝ ወጥ እና
ሥርዓት ያለው አወጋገድ እንደሌለ ነው የተጠቆመው። በመሆኑም አገልግሎት የሰጡ የህክምና መሳሪያዎች ዳግም ጥቅም ላይ
ቢውሉ በምን ማረጋገጥ ይቻላል? የሚለው ጥያቄ አነጋጋሪ ሆኗል።
የቤተል ቲቺንግ ጄኔራል ሆስፒታል ማኔጂንግ ዳይሬክተር ዶክተር ይገረሙ አስፋው፤ «ሌሎች
የህክምና ተቋማት መወገድ ያለባቸውን የህክምና ቁሶች መልሰው ጥቅም ላይ ስለማዋላቸው ማረጋገጫ የለኝም። ይሁንና
በሆስፒታላችን በኩል ግን ለአንድ ጊዜ የሚውሉትን ዳግም አገልግሎት ላይ የማዋል ችግር እንደማይከሰት ማረጋገጥ
እችላለሁ» ይላሉ።
በህክምና ተቋማት ውስጥ የሚገኙ መሳሪያዎች ለአንድ ጊዜ ብቻ ጥቅም የሚሰጡ እና ወዲያው መወገድ ያለባቸው እንዲሁም
በተደጋጋሚ ጥቅም ላይ ውለው በየጊዜው ከተህዋሲያን እንዲጸዱ የሚታከሙ መሳሪያዎች መኖራቸውንም ይጠቁማሉ።
ለአንድ
ጊዜ ጥቅም ላይ የሚውሉ እንደ መርፌ እና የህክምና ጓንት የመሳሰሉት አገልግሎት ከሰጡ በኋላ በሆስፒታሉ
በተዘጋጀላቸው ቦታ ላይ እስከሚቀልጡ ድረስ በከፍተኛ ሙቀት እንደሚቃጠሉ ነው የሚያስረዱት። በመሆኑም ዳግም ጥቅም
ላይ ለማዋል ሙያው የማይፈቅድ እና የሰዎች ጤና ላይ የሚያደርሰው ጉዳት የከፋ በመሆኑ ተቋሙ በራሱ የማቃጠያ ቦታ
እንደሚያስወግዳቸው ነው የሚገልፁት። በዚህ ረገድ ውድ የሚባሉትን መሳሪያዎች ጭምር ህጉ በሚፈቅደው መንገድ
እንደሚያስወግዱ ነው የጠቆሙት። ለአብነትም ኩላሊትን ተክቶ በሚሰራ ማሽን ላይ ለአንድ ሰው የሚያገለግል መሳሪያ
ጥቅም ላይ ከዋለ በኋላ ወዲያውኑ እንደሚወደግ ያስረዳሉ።
«የተለያዩ የህክምና ተቋማት ወጥነት የሌለው የቆሻሻ አወጋገድ ባለመከተላቸው የተነሳ በርካታ ያገለገሉ የህክምና መሳሪያዎች በየጓሮው ተከማችተው ይገኛሉ» የሚሉት ደግሞ በየካቲት 12 ሜዲካል
ኮሌጅ ረዳት ፕሮፌሰር ዳንኤል አበበ ናቸው። በአሁኑ ወቅት ተግባራዊ እየተደረገ በሚገኘው እያንዳንዱ የህክምና
ተቋም ጽዱ እና ምቹ ማድረግ አላማው ያደረገ ፕሮግራም ተዘርግቷል። በመሆኑም በየተቋማቱ የተከማቹት መርፌና ጓንትን
ጨምሮ የተለያዩ የህክምና ቁሶች መወገድ እንደሚገባቸው ነው የሚናገሩት።
«የህክምና መርፌዎች ከተላላፊ በሽታዎች ጋር በተያያዘ መልሰው ጥቅም ላይ መዋል የለባቸውም» የሚለውን
ሃሳብ የሚደግፉት ረዳት ፕሮፌሰሩ፤ ይልቁንም ባለሙያዎች መርፌውን ሲከፍቱ እንኳን መሬት ላይ ቢወድቅባቸው በቆሻሻ
ማጠራቀሚያ ውስጥ መጨመር እንደሚገባ ነው የሚገልፁት። ይሁንና ፕላስቲክ እና ብረት ነክ የህክምና መሳሪያዎች ማቃጠል
የማይገባ በመሆኑ መቅበር እንደሚያስፈልግ ነው የሚጠቁሙት። ይህንን ሁሉም የህክምና ተቋማት በአግባቡ ይተገብሩታል
የሚለው ጉዳይ ላይ ግን እርግጠኛ እንደማይሆኑ ነው የሚናገሩት።
በቀድሞ
ጊዜ የዘውዲቱ ሆስፒታል ኃላፊ በነበሩበት ወቅት ለአስር ዓመት የተከማቹ አገልግሎት የማይሰጡ የህክምና ቁሶች እና
መድኃኒቶችን በኮሚቴ አማካኝነት በተመረጠ አካባቢ እንደተቃጠሉ ያስታውሳሉ። በየካቲት 12 ሆስፒታልም
በተመሳሳይ የተከማቹ ቁሶች እንደሚገኙ ነው የሚያስረዱት። ይሁንና ይህ ማለት ግን መልሰው አገልግሎት ላይ እየዋሉ
ነው ማለት እንዳልሆነም ነው የሚገልፁት። ሆስፒታሉም ጥቅም ላይ ውለው የሚከማቹትን ቁሶች በዘመናዊ ማሽን አማካኝነት
ለማስወገድ ፍቃድ ለማውጣት በሂደት ላይ እንደሚገኝ ይጠቁማሉ። ይህንንም ተግባራዊ በማድረግ «የተጣሉ መሳሪያዎች ዳግም ጥቅም ላይ ሊውሉ ይችላሉ» የሚለውን ጥርጣሬ ሙሉ በሙሉ ማስቀረት እንደሚቻል ነው የሚጠቁሙት።
የኢትዮጵያ
የምግብ፣ መድኃኒትና የጤና ክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለስልጣን የመድኃኒት ተቋማት ኢንስፔክሽን ዳይሬክተር አቶ
ገዛኸኝ እንዳለ በበኩላቸው፤ ከበርካታ ዓመታት በፊት የህክምና መርፌዎች ከተቀቀሉ በኋላ ጥቅም ላይ ይውሉ
እንደነበር ያስታውሳሉ። በአሁኑ ወቅት ግን የተላላፊ በሽታዎች ከመስፋታቸው የተነሳ ይህ ዓይነት አሰራር
እንደማይፈቀድ ይናገራሉ። በመሆኑም ብረት ነክ የሆኑ የህክምና መሳሪያዎች አገልግሎት እንደማይሰጡ ከተረጋገጠ ለብረት
አቅላጭ ተቋማት ማቅረብ እንደሚገባው ነው የሚናገሩት። ባለስልጣኑም በአወጋገዱ ላይ ለጤና ተቋማት አሰራር
የመዘርጋት እንጂ ወደ እያንዳንዱ ተቋም ወርዶ ቁጥጥር ማድረግ እንደማይችል ነው ያሳሰቡት። ይሁንና እስካሁን መልሶ
ጥቅም ላይ የሚያውል የጤና ተቋም ባይከሰትም ሲገኝ ግን አስፈላጊው ህጋዊ እርምጃ እንደሚወሰድበት ነው
የሚያረጋግጡት።
በህዝብ
ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ወጪ አስተዳደርና ቁጥጥር ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አምባሳደር መስፍን ቸርነት፤
አገልግሎት የሰጡ የህክምና ቁሶች መልሰው ጥቅም ላይ ለማዋል የሚደረግ ቁጥጥር ባለመኖሩ ጉዳዩ እንደሚያሳስባቸው
ይጠቁማሉ። «መወገድ
ያለባቸው የህክምና መሳሪያዎች በአግባቡ ይወገዳሉ የሚለው ጥብቅ ቁጥጥር የለውም። በዚህም በህገወጥ መንገድ
ለመክበር የሚፈልጉ አካላት መልሰው አገልግሎት ላይ ሊያውሉት አይችሉም ብሎ መከራከር አይቻልም» የሚል እምነት አላቸው።
እንደ
አምባሳደር መስፍን ገለጻ፤ አደገኛ ኬሚካሎችን እና መድኃኒቶችን ጨምሮ ልዩ ክትትል የሚያስፈልገው ይህን ጉዳይ
በተመለከተ ፓርላማው ባለፈው ዓመት ለጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ጥያቄ አቅርቦ ነበር። በወቅቱም አንድ
ኃይል ተቋቁሞ ችግሩ እልባት እንደሚያገኝ አቅጣጫ ተሰጥቷል። በመሆኑም የህክምና ቁሶች የገቡበት እና ጥቅም ላይ
የዋሉበት ጊዜ በየተቋማቱ ተመዝግቦ የሚያዝ በመሆኑ የሚወገዱበት ወቅትም ማጣራት ይቻላል። እናም መልሰው ጥቅም ላይ
ቢውሉ ሊደርስ የሚችለውን ጉዳት በማሰብ አወጋገዱን ስርዓት ማስያዝ ብሎም ጥብቅ ቁጥጥር ማድረግ የግድ የሚያስፈልገው
አገራዊ ጉዳይ መሆኑን ነው አምባሳደር መስፍን አፅንኦት ሰጥተው ያሳሰቡት።








